ባሕርዳር፡ ጥቅምት 10/2013 ዓ.ም (አብመድ) ከአውሮፓውያኑ 1993 ጀምሮ ሱዳን ሽብርተኝነትን ከሚደግፉ ሀገራት ስም ዝርዝር ውስጥ ተካታለች፡፡ ይህም የቀድሞው የአልቃይዳ መሪ ኦሳማ ቢንላደን የመንግስት እንግዳ ሆነው መኖራቸውን ተከትሎ የመጣ ነው፡፡
የካሳ ክፍያው በአውሮፓውያኑ 1998 የአሜሪካ ኢምባሲ ላይ በአልቃይዳ ጥቃት ከመፈፀሙ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ በኬንያና ታንዛኒያ የተፈፀሙት ጥቃቶች ከ2 መቶ በላይ ሰዎች ህይወታቸውን አጠውበታል፡፡
ሱዳን 3 መቶ 35 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ካሳ ከከፈለች በሀገራት ከሚደገፍ ሽብርተኝነት ስም ዝርዝር ውስጥ እንደሚያስወጡ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተናግረዋል፡፡
የሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር አብደላ ሀምዶክ ገንዘቡ እንደተዛወረ አስታውቀዋል፤ነገር ግን በአሜሪካ በኩል ወዲያውን የመጣ የማረጋገጫ ምላሽ እንደሌለ ጠቁመዋል፡፡
እንደ ቢቢሲ ዘገባ የካሳ ክፍያው ለአሜሪካውያን የሽብር ተጠቂዎችና ቤተሰቦቻቸው የሚከፈል መሆኑን ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናግረዋል፡፡
በኪሩቤል ተሾመ