ጥቅምት 11/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የኢትዮ – ኬንያ ባለ 500 ኪሎ ቮልት የከፍተኛ ኃይል ማስተላለፊያ መስመር በቀጣዮቹ ሁለት ሳምንታት ኃይል ማስተላለፍ ይጀምራል።
ኅብረተሰቡ ከኃይል ማስተላለፊያ መስመር ተሸካሚ የብረት ምሰሶዎች ንክኪ እንዲርቅም ተጠይቋል።
በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የማስተላለፊያ መስመሮችና ማከፋፈያ ጣቢያዎች ኮንስትራክሽን ዘርፍ ሥራ አስፈጻሚ ክብሮም ካህሳይ ከወላይታ ዞን አሥተዳዳሪና የመምሪያ ኃላፊዎች ጋር ውይይት አካሂደዋል፡፡
በውይይቱ ለሁለቱ ሀገራት የኃይል ትስስርና ለኢኮኖሚ ያለው ፋይዳ የላቀ መሆኑን ለአመራሮቹ ገልጸዋል፡፡
በተመሳሳይ በጋሞ ዞን በኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት ላይ የሚፈጸመው ስርቆት እየቀነሰ ቢመጣም አሁንም ክትትል የሚያስፈልገው ስለመሆኑ ተገልጿል፡፡
በቀጣይም በዞኑ መሠረተ ልማቱ በሚያልፍባቸው አካካቢዎች ምንም ዓይነት ስርቆት እንዳይከሰት ለኅብረተሰቡ ግንዛቤ የማስጨበጥ ሥራ እንዲሠራ፣ የፀጥታ አካላትም ተንቀሳቅሰው እንዲጠብቁና ኅብረተሰቡ በይዞታው ላይ የተተከሉትን ምሰሶዎች እንዲጠብቅ ግንዛቤ የማስጨበጥ ሥራ እንዲያከናውን ጥያቄ ቀርቦ መግባባት ላይ ተደርሷል፡፡
በጋሞ ዞን ምዕራብ አባያ ወረዳ 18 ቤቶች ካሳ ተከፍሏቸው አለመነሳታቸው በውይይቱ ላይ ተጠቅሷል፡፡
በተያያዘ ዜና በፕሮጀክቱ ሥራ መጀመር ዙሪያ ከኦሮሚያ ክልል ርእሰ መሥተዳድር ጽሕፈት ቤት የሥራ ኃላፊዎች ጋር ውይይት መደረጉን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል መረጃ ያመላክታል።
ለሀገር ክብር በትግል እናብር‼