ባሕር ዳር:መጋቢት 10/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የአዕምሮ እድገት ውስንነት (ዳውን ሲንድረም) የተዘነጋ ነገር ግን ልዩ ትኩረት የሚፈልግ መሆኑን የኢፌዴሪ ፕሬዚደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ገለጹ።
ዓለም አቀፉ የአዕምሮ እድገት ውስንነት (የዳውን ሲንድረም) ቀን “ስለ እኛ ከኛ ጋር” በሚል መሪ ሃሳብ በዲቦራ ፋውንዴሽን አዘጋጅነት በወዳጅነት ፓርክ እየተካሄደ ነው።
በመርኃ ግብሩ ፕሬዝደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ፣ የጤና ሚንስትር ዶክተር ሊያ ታደሰ እና የዲቦራ ፋውንዴሽን መስራች አቶ አባዱላ ገመዳ ተገኝተዋል።
በመርኃ-ግብሩ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት ፕሬዚደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ “የአዕምሮ እድገት ውስንነት የተዘነጋ ነገር ግን ልዩ ትኩረት የሚፈልግ ነው” ብለዋል።
ኅብረተሰቡ ይህንን ችግር በመረዳት ለእነዚህ የኅብረተሰብ ክፍሎች ዕድል መስጠት እንደሚባ ፕሬዚደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ አስገንዝበዋል።
ቀኑ ከአንድ ቀን ባለፈ ዓመቱን ሙሉ ሊሰራበት የሚገባ መሆኑን አመላክተዋል።
የጤና ሚንስትሯ ዶክተር ሊያ ታደሰ በበኩላቸው የአዕምሮ እድገት ውስንነት ሰፊ ትኩረት የሚጠይቅ ነገር ግን ብዙ ያልተሰራበት መሆኑን ተናግረዋል።

በዚህ ችግር ውስጥ ላሉ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት በሚኒስቴሩ የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ጠቁመዋል።
የአዕምሮ እድገት ውስንነት ያለባቸው ዜጎች እንደማንኛውም ዜጋ ሀገራቸውን የሚጠቅሙ ናቸው ያሉት ደግሞ የዲቦራ ፋውንዴሽን መስራች አቶ አባዱላ ገመዳ ናቸው።
ፋውንዴሽኑ ሀገራቸውን የሚያኮሩ ትውልድን መፍጠር ዓላማ አድርጎ በዚህ ችግር ውስጥ ያሉ ዜጎችን እያገዘ ይገኛል ብለዋል።
ዓለም አቀፉ የአዕምሮ እድገት ውስንነት (የዳውን ሲንድረም) ቀን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ከ2012 ጀምሮ በይፋ የሚከበር የግንዛቤ ማስጨበጫ ቀን ነው።
ቀኑ የአዕምሮ እድገት ውስንነት ያለባቸው ሰዎች መብት፣ ማካተት እና ደህንነትን የሚደግፍ አንድ ዓለም አቀፍ ድምጽ የተፈጠረበት ቀን መሆኑም ተገልጿል።
ቀኑ “ስለ እኛ ከኛ ጋር” በሚል መሪ ሃሳብ በኢትዮጵያ ለሶስተኛ ጊዜ እየተከበረ መሆኑ በመርኃ ግብሩ ላይ ተገልጿል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!