የብዙዎችን ሕይዎት የለወጠው “ነጭ ወርቅ” – እጣን !

178
👉በ2014 ዓ.ም 1 ኩንታል እጣን እስከ 23 ሺህ ብር ተሽጧል
ገንዳ ውኃ፡ መጋቢት 18/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ምዕራብ ጎንደር ዞን አጠቃላይ ካለው የደን ሽፋን 30 በመቶው በእጣን ዛፍ የተሸፈነ ነው።
ይሕ ሃብት ተገቢውን ጥቅም ሳይሰጥ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተመናመነ እንደሚገኝ ነው በመተማ ወረዳ ለምለም ተራራ ቀበሌ በእጣንና ሙጫ ማምረት የተደራጁ ወጣቶች ለአሚኮ የተናገሩት።
በእጣንና ሙጫ ማምረት ላይ ያገኘናቸው የኑስ ዲቦ እንዳሉት ከሃብቱ የሚገኘው ገቢ ከሰሊጥ፣ ጥጥና ማሽላ ምርት ከሚገኘው ገቢ በአስር እጥፍ ብልጫ አለው። በ2014 ዓ.ም 1 ኩንታል እስከ 23 ሺህ ብር ለገበያ ማቅረብ መቻሉን ነው ለአብነት ያነሱት።
በዚህም የአብዛኛው የማኅበሩን አባላት ሕይወት መለወጡን ነው የገለጹት።
ሌሎች ያነጋገርናቸው የማኅበሩ አባላትም የእጣን ዛፍ ያለውን ኢኮኖያዊ ጠቀሜታ በመረዳት ከሰደድ እሳትና ከደን ጭፍጨፋ ጥበቃ እያደረጉ መኾናቸውን ነግረውናል።
በምዕራብ ጎንደር ዞን አካባቢና ደን ጥበቃ ጽሕፈት ቤት የአካባቢ ሕግ ተከባሪነትና የአካባቢ ማኅበረሰብ ተጽዕኖ ግምገማ ቡድን መሪ ሀብታሙ አድጎ፤ ምዕራብ ጎንደር ዞን ካለው 760 ሺህ ሄክታር መሬት የሚጠጋ የደን ሽፋን ውስጥ ከ230 ሺህ በላይ የሚኾነው በእጣን ዛፍ የተሸፈነ መኾኑን ገልጸዋል።
ታዲያ ይህ ሃብት ባለፉት ዓመታት በተለያዩ ችግሮች ምክንያት በሚጠበቀው ልክ ጥቅም ላይ አለመዋሉን ነው ያነሱት።
👉 በ2014 በጀት ዓመት በዞኑ በተሠራው ሥራ 4 ሺህ 80ዐ ኩንታል የሚጠጋ እጣንና ሙጫ ተመርቷል።
👉 ከ67 ሚሊዮን ብር በላይ ደግሞ ገቢ ተገኝቷል።
👉በ2015 ዓ.ም ከ9 ሺህ ኩንታል በላይ የእጣንና ሙጫ ምርት የመሰብሰብ ሥራ እየተከናወነ ይገኛል።
👉 ከ163 ሚሊዮን ብር በላይ ደግሞ ገቢ ለማግኘት ታቅዷል።
👉 22 ማኅበራትና 24 ባለሃብቶች በእጣንና ሙጫ ማምረት ፈቃድ ወስደው ወደ ሥራ ገብተዋል።
👉በዞኑ ያለውን ሃብት በሙሉ አቅም ማምረት ቢቻል በዓመት ከ35 ሺህ በላይ ኩንታል የእጣንና ሙጫ ምርት ማግኘት ይቻላል።
👉ይሕም አሁን ባለው ዋጋ እንኳ ለገበያ ቢቀርብ 609 ሚሊዮን ብር ዞኑ ገቢ ማግኘት ይችላል።
አቶ ሀብታሙ እንዳሉት የእጣን ዛፍ ለረጅም ጊዜ አገልግሎት እንዲሰጥ አምራቾች በዘመናዊ ማምረቻ መሳሪያ እንዲያመርቱ ተደርጓል፤ ባለሙያዎችም የአመራረት ሂደቱን ክትትልና ድጋፍ እያደረጉ ይገኛሉ፤ የሕገ ወጥ እርሻ መስፋፋት፣ ሰደድ እሳት እና ሌሎች ችግሮችን ለመከላከል የጥበቃ ሥራ ላይ ትኩረት ተደርጓል፤ በተለይም ደግሞ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ዋጋው እየጨመረ በመምጣቱ የአካባቢው ማኅበረሰብ ጥበቃ እየተጠናከረ መምጣቱንም አንስተዋል።
ዘጋቢ፦ ዳግማዊ ተሠራ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!