አዲስ አበባ: ሚያዝያ 24/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር በሀገሪቱ ውስጥ ለሚገኙ የክልል ከተሞችና ከተማ አሥተዳደሮች እንዲዘምኑ ራሳቸው እንዲችሉና ለነዋሪዎች ምቹ እንዲኾኑ ሥልጣን በተሰሠጠው መሰረት በርካታ ሥራዎችን እየሠራ ይገኛል፡፡
ከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር ከክልሎች እና ከከተማ አሥተዳደር ጋር በልማትና በአጠቃላይ ሥራዎች ያላቸው ቁርኝት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረና ሚኒስቴር መሥረያ ቤቱ ከክልሎች አስፋላጊውን ድጋፍ ያደርጋል ነው ያሉት ሚኒስትሯ ጫልቱ ሳኒ። በዚህም መሰረት በመስክ ምልከታ የሚዛን አማን ከተማ አሥተዳደር ከሌሎች ከተሞች በአረንጓዴ ልማት የተሻለ ኾኖ በመገኘቱ ዘመናዊ የከተማ ፓርክ እንዲሠራ ወሰነናል ብለዋል፡፡
ከሚኒስቴር መሥርያ ቤቱ የከተማ ማስፋፊያ ፕሮጀክት መሰረት ለሚዛን አማን ከተማ አሥተዳደር የ10 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ማድረጋቸውን ገልጸው ከተማ አሥተዳደሩ ከተማውን የሚመጥን ፓርክ እንዲሠራ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡
የሚዛን አማን ከተማ አሥተዳደር ከንቲባ ግሩም ተማም ፕሮጀክቱ የከተማው ሕዝብ ጥያቄና ፍላጎት በመኾኑ መደሰታቸውን ገልጸዋል።
ከተማና መሰረት ልማት ሚኒስቴር ከክልሎች ጋር በመተባበር የከተሞች ልማት ከገጠር ልማት ጋር በተቀናጀ መንገድ የሚከናወንበትን ኹኔታ በሚመለከት ጥናቶችን ማድረግ፤አፈጻጸማቸውንም መከታተል፤ከተሞች የአካባቢያቸው የልማት ማዕከል እንዲኾኑ ሁለ-ገብና የተቀናጀ ድጋፍ መስጠት ሥራዎችን ይሠራል በማለት ወይዘሮ ጫልቱ ሳኒ ገልጸዋል፡፡
ዘግቢ:- ሳሙኤል ኪሮስ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!