ባሕርዳር: መጋቢት 06/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ኢትዮጵያ እና አሜሪካ በልማት እና የዴሞክራሲ ግንባታ ስራዎች እና መሰል ጉዳዮች ላይ መምከራቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ።
የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር መለስ ዓለም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ጋር ያደረጉትን ውይይት አስመልክቶ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
ቃል አቀባዩ በመግለጫቸው ሚኒስትሮቹ በሁለትዮሽ እና ቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ መምከራቸውን አንስተዋል።
በፕሪቶሪያ እና በናይሮቢ ከተደረሰው የሰላም ስምምነት በኋላ ያሉ የአፈጻጸም ሂደቶች፣ በልማት እና የዴሞክራሲ ግንባታ በሚሠሯቸው ሥራዎች እና መሰል ጉዳዮች ላይ ሁለቱ ሀገራት መምከራቸውንም ገልጸዋል።
የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን በኢትዮጵያ ይፋዊ የሥራ ጉብኝት እያደረጉ ይገኛሉ።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!