ደሴ: መጋቢት 06/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በደቡብ ወሎ ዞን የካቲት 30/2015 ዓ.ም በረዶ ቀላቅሎ በጣለዉ ዝናብ ምክንያት ከ450 ሚሊየን ብር በላይ ግምት ያለው ሀብት ወድሟል።
በሠብሎቻቸውና በአትክልቶቻቸው ላይ ውድመት የደረሰባቸው አርሶ አደሮችም የደረሠው ጉዳት ከፍተኛ በመሆኑ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠይቀዋል።
የደቡብ ወሎ ዞን አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ተጠሪ ጽሕፈት ቤት ኀላፊ አቶ ኢብራሒም ይመር እንደገለፁት በዞኑ በሚገኙት አምባሠል፣ ቃሉ፣ አልብኮና ተሁለደሬ ወረዳዎች በረዶ ቀላቅሎ በጣለው ዝናብ በ571 ሄክታር መሬት ላይ ያሉ የተለያዩ የመስኖ ሠብሎች፣ የመኖሪያ ቤቶች፣ አትክልትና ፍራፍሬ ላይ ከፍተኛ ውድመት መድረሱን ገልፀዋል።

የደረሠው ጉዳት ከፍተኛ በመሆኑ በጉዳቱ ለተጋለጡ የኀብረተሰብ ክፍሎች አስቸኳይ ምግብ፣ መጠለያና አልባሳት በማስፈለጉ የድጋፍ ጥሪ አስተላልፈዋል።
ዘጋቢ:–ቤቴል መኮንን
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!