ባሕር ዳር፡ ነሐሴ 8/2012 ዓ.ም (አብመድ) የኮሮናቫይረስ ስርጭት በዚህ ከቀጠለ ከስሃራ በታች ባሉ የአፍሪካ ሃገራት ከ13 እስከ 15 ሚሊየን የሚደርስ ሕዝብ ለከፋ ድህነት ሊጋለጥ እንደሚችል የዓለም ባንክ አስጠንቅቋል።
በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት በአፍሪካ የሥራ አጥ ቁጥር መጨመሩን የዓለም ባንክ አስታውቋል፡፡ የዓለም ባንክ በስልክ ሰበሰብኩት ባለው መረጃው በአፍሪካ በሕዝብ ብዛት ቀዳሚዋ ናይጄሪያ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሳቢያ 42 በመቶ ዜጎቿ ከሥራ ሲሰናበቱ 79 በመቶ የሚሆኑ ዜጎቿ ደግሞ ገቢ እንደቀነሰባቸው አመላክቷል፡፡
የዓለም ባንክ ከአህጉሩ በሕዝብ ብዛት ሁለተኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው ኢትዮጵያም 45 በመቶው ከተሜ እና 55 በመቶው የገጠር ነዋሪ በቫይረሱ ስርጭት ምክንያት የገቢ መቀነስ እንደተፈጠረበት በስልክ በሰበሰብኩት መረጃ አረጋግጫለሁ ብሏል፡፡
የዓለም ባንክ የችግሩን አሳሳቢነት ሲገልፅም የቫይረሱ ስርጭት በዚሁ ከቀጠለ ከሰሃራ በታች ባሉ የአፍሪካ ሃገራት ከ13 እስከ 15 ሚሊዮን የሚደርስ ሕዝብ ለከፋ ድህነት ሊጋለጥ ይችላል በማለት አስጠንቅቋል፡፡
ምንጭ፡- ሲ ጂ ቲ ኤን
በታዘብ አራጋው