ባሕር ዳር፡ ጥቅምት 30/2013 ዓ.ም (አብመድ) የክልላችንን ህዝብ ስነልቦና አብሮ ለትልቅ ግብ ስኬት እንዴት መጓዝ እንዳለብን ለማስተማር አይዳዳኝም ያሉት አቶ ተመሥገን በሀገራችን አሻራ ላይ ግዙፉን አብሮነት በተግባር ያረጋገጠ ማኅበረሰብን ማገልገል በራሱ ትልቅ ትምህርትና መታደል ነው ብለዋል።
በአማራ ክልላዊ መንግስት ከፍተኛ አመራርነት ሳገለግል ለራሴ ያሳመንኩት ይህንኑ በመርህ እና ተግባር የጸናውን አብሮነት ባህል በአመራርነት ጥበባችን በማስረጽ መተጋገዝ ይገባናል ነው ያሉት። ሁላችንም ለቆምንለት አላማ ለተሰጠን ሀላፊነት “የጦር ጀነራል ነን” በሚል ዋናው ስራችን ላይ ማተኮርን መምረጥ እንደሚገባ ተናግረዋል።
በአማራ ክልላዊ መንግስት ፕሬዝዳንትነት የነበረኝ ቆይታ እጅግ መልካም የሚባል ነበር ብለዋል። ቆይታዬ መልካም እንዲሆን ያገዛችሁኝ በየደረጃው ያላችሁ አመራሮችና መላው የክልሉ ህዝብ ምስጋናዬን አቀርባለሁ፤ በቀጣይም በብዙ ኃላፊነቶች እንደምንገናኝ ተስፋ አደርጋለሁ ነው ያሉት።
አቶ ተመሥገን በይፋዊ የማህበራዊ ገፃቸው ለሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ ድልና ሰላምን ተመኝተዋል፡፡